Saturday, February 15, 2014

የጉባኤው ጥቅም ወይስ የአባ ሰረቀ ደብዳቤ?



 የአባ ሰረቀ ደብዳቤ ማኅበረ ቅዱሳን ለአብነት መምህራን ለታላቅ ዓላማ ያዘጋጀውን ሀገር አቀፍ የምክክር ጉባኤ እንዲታገድ ምክንያት ሆነ። ጉባኤው ለቤተ ክርስቲያን የሚሰጠውን ሁለተናዊ ጥቅም ወደጎን በመተው ምንም ረብ ለሌለው ደብዳቤ ቅድሚያ በመስጠት ጉባኤው እንዲታገድ የመንግሥት/ፖሊስ እገዛን መጠየቅ ቤተ ክርስቲያንን ያስተዳድራሉ ይመራሉ ተብለው ከሚጠበቁ ብፁዓን አባቶች ቀርቶ ከአንድ የቤተክርስቲያን ምእመን የሚጠበቅ ተግባር አልነበረም አይደለምም።
የጉባኤው አላማ ለማንም የተሰወረ አልነበረም። በማኅበረ ቅዱሳን አሰራርም የሚያከናውናቸውን መንፈሳዊ ተግባራት ሁሉ አስቀድሞ ከጠቅላይ ቤተ ክህነት እስከ ቅዱስ ሲኖደስ ድረስ አሳውቆና ምክር ጠይቆ እንደሚሰራ ይታወቃል። በዚህም መሰረት ይህም የምክክር ጉባኤ ቀደም ብሎ የታቀደና መቼ፣ እንዴትና በምን ዙርያ እንደሆነ አባ ሰረቀም እራሳቸው በሚገባ ያውቁታል።

በእርግጥ የአባ ሰረቀና የማኅበረ ቅዱሳን የአለመግባባት ጉዳይ ዛሬ የተከሰተ እንግዳ ነገር አይደለም፤ ለአመታት የዘለቀ፣ የሰ/ት ት/ቤቶች ማደራጃ መምርያ ኃላፊ በነበሩበት ጊዜ የማኅበሩን አገልግሎት ሙሉ ለሙሉ እስከማስቆም ድረስ ጽኑ አላማ ይዘው ሲንቀሳቀሱ እንደነበር እና ተመሳሳይ ደብዳቤዎችን ይጽፉ እንደነበር መቼም የማይረሳ የዘወትር ትዝታ ነው።
አባ ሰረቀ በኃላፊነት የያዙትን መምርያ/የሰ/ት/ቤቶች ማ/መምርያ በትክክል ባለመምራታቸው፣ ለማኅበረ ቅዱሳንም መንፈሳዊነቱን የለቀቀ የእግድና የማስጠንቀቃ ደብዳቤ በተደጋጋሚ በመጻፋቸው እና ሌሎች ከአንድ መንፈሳዊ መሪ ነኝ ከሚል አባት የማይጠበቁ ተግባራትን ምክንያት በማድረግ በ2004 ዓም በተካሄደው የጥቅምቱ ቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ ከመምርያ ኃላፊነታቸው እንዲወርዱ በመወሰኑ ከሥልጣናቸው በአስቸኳይ እንደለቀቁ የማይዘነጋ ሃቅ ነው። በዚሁ ጉባኤም የእምነት ችግር አለባቸው ተብሎ በሚከሰሱበት ከኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ እምነት ውጪ ነው የሚባለውን እምነታቸውን የሚመረምር ሊቃነ ጳጳሳት የሚገኙበት ኮሚቴ ተቋቁሞ እንደነበርም ይታወሳል። እንዲህ አይነት ሰዎችን ግን በመምርያ ኃላፊነት ማስቀመጥ በራሱ ለቤተ ክርስቲያን የሚፈጥረውን ችግር ቅዱስ ሲኖዶስ ቢመለከተው መልካም ነው።
በአንጻሩ ማኅበረ ቅዱሳን ደግሞ ቅዱስ ሲኖዶስ የሰጠውን ኃላፊነት ለመወጣት እውቀቱን፣ ገንዘቡንና ጉልበቱን ለቤተ ክርስቲያን በመስጠት ቤተ ክርስቲያንን ለማገዝ ደፋ ቀና የሚል ማኅበር ነው። ስብከተ ወንጌልን በማስፋፋት፣ የአብነት ት/ቤቶችንና ገዳማትን በመርዳት፣ ምእመናን በምክረ አበው ተጠቃሚ እንዲሆኑ በማድረግ፣ የተለያዩ የውይይትና ምክክር ጉባኤያትን በማድረግ ለቤተ ክርስቲያን የበኩልን ድርሻ በመወጣት ላይ የሚገኝ ማኅበር ነው።

ቅዱስነታቸው ይህን ጉዳይ ሳይረዱና ሳይመረምሩ የቤተ ክርስቲን አይን እና ጀሮ የሆኑትን ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንን ማኅበረ ቅዱሳን እንድትወያዩ፣ እንድትመካከሩ፣ በአካል እንድትገናኙ ማድረጉ ስህተት ነውና ተመልሳችሁ ሂዱ፣ ልፋታችሁ፣ ድካማችሁ ከንቱ ይሁን ብለው የእግድ ደብደቤ መጻፋቸው በእውነት ምክንያቱ ተሰውሮብኛል። በእየ ገዳማቱ የሚገኙ ሊቃውንት ምክራቸው የማይሰለች፤ቃላቸው የማይጠገብ አንደበተ ርዕቱ አባቶቻችንን ዛሬ ምነው በአደባባይ እንዳይመክሩን ታገዱ??? ምነው ቅዱስነትዎ ለቤተ ክርስቲያን የደም ሰማዕትነትም ቢሆን መስጠት የሚችሉ አባቶቻችንን እንዳይናገሩ፣ እንዳይወያዩ አደረጉ? እንዴት ከጉባኤው ጥቅም ይልቅ የአባ ሰረቀ ረብ የለሽ ነጠላ ደብዳቤ ሚዛን ደፋ?

ዛሬ ላይ የቤተ ክርስቲያኗ ትልቁ ችግር እንደ አባ ሰረቀ እና መሰል ችግር ፈጣሪ ሰዎችን የመምርያ ኃላፊ፣ የአድባራትና ገዳማት እንዲሁም የአጥቢያ ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪ ተደርገው መሾማቸው ነው። ከአጥቢያ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ጀምሮ እስከ ጠቅላይ ቤተ ክህነት የመምርያ ሰራተኞች በእየዘርፉ ችግር ፈጣሪ አካላት አሉባት። ቅዱስ ሲኖዶስ ይህን ችግሯን ሊረዳላት ይገባል። እንዲህ አይነት ሰዎችን በማነኛውም መመዘኛ በኋላፊነት መመደቡ ለቤተ ክርስቲያን ውድቀት እንጂ ለውጥና እድገት አይመጣም።


ማኅበረ ቅዱሳን እኮ አባ ሰረቀ የሚመሩት የመምርያ ክፍል በዋናነት በእቅድ ይዞ ሊሰራው የሚገባውን ተግባር በጀት ሳይጠይቅ በራሱ በጀት ሊቃውንቱን ለውይይት መጋበዙ ምስጋና ያስችረው  ነበር እንጂ ጉባኤውን ለማሳገድ ብዕር አያስነሳም ነበር። እንዲሁም በትብብር አብሮ ለመስራትና የሊቃውንቱን ምክር ለመቀበል በጋራ ማስኬድ ት መልካም አጋጣሚ ነበር። ግን ምን ዋጋ አለው ቅናዊ አስተሳሰብ ጠፋ፣ ሁልግዜም የማኅበሩን አገልግሎት ለማዳከም እንቅልፍ በአይናቸው አልዞር ያላቸው እኒህ አባት ሊቃውንቱን አሳዘኑ። ማኅበሩ ግን የአባቶች በረከት አልቀረበትም ይልቁንም በእንዲህ አይነት አባት ነን ባዮች እየተፈተነ እንደሚያገለግል ገዳማውያን አባቶቻች በሚገባ እንዲረዱና በጸሎታቸው እንዲያስቡት ጥሩ ምክንያት ሆነለት።  

ቅዱስነታቸውም ቢሆን የጉባኤውን ዓላማና አስፈላጊነት በሚገባ እያወቁና እየተረዱ ለማይሰራና ለማያሰራ የመምርያ ኃላፊ እኔ መሥራት ያላብኝን ተግባር ማኅበረ ቅዱሳን አከናወኑብኝ በሚል ተልካሻ ምክንያት ለተጻፈ ደብዳቤ ቅድሚያ ሰጥተው ሊቃውንቱ እንዲበተኑ ማድረጋቸው ምናልባትም በዘመነ ፕትርክናቸው ከሰሩት ሥራዎች ለታሪክ መጥፎ አሻራ ይሆንባቸው ይሆናል። እንዲያ ባይሆን ኑሮማ ደብዳቤ እንደ ደረሳቸው ሁለቱንም ጠርተው አባታዊ ቡራኬና ምክር ሰጠው ጉባኤውን በጋራ በመተባበር እንዲካሄድ ማድረግ ይችሉ ነበር። ወይም ጉባኤው ከተካሄደ በኋላ ለማኅበሩ ይህን ጉባኤው የትምህርትና ሓዋርያዊ አገልግሎት ስልጠና መምርያ ማለትም አባ ሰረቀ በሃላፊነት ሊያከናውኑት እንደሚችሉ መልእክት ማስተላለፍ ይችሉ ነበር።  

አባቶቻችን ሆይ እኛ በዓለም የምንኖር ልጆቻችሁ በዚህ እና መሰል ፈተናወች ውስጥ ነውና ያለን በጸሎታችሁ አስቡን አትርሱን! መቻሉን፣ ትግዕስትን፣ አስተዋይነትን እንዲያድለን ለምኑልን!
ቤተ ክርስቲያንን እንመራለን እናስተዳድራለን ለሚሉ ሁሉ መልካም መሪ እንዲሆኑ ጸልዩላቸው!


EOTC Radio "ወቅታዊ ጉዳይ" ስለ ሦስተኛው ሀገር አቀፍ የአብነት መምህራን ጉባኤ መታገድ
Hara tewahdo;ማኅበረ ቅዱሳን ለአብነት መምህራን ያዘጋጀው ሀገር አቀፍ የምክክር ጉባኤ ታገደ
http://www.danielkibret.com/2014/02/blog-post_14.html